ብፁዕ አቡነ ናትናኤል በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ኢየሩሳሌም ሲደርሱ ደማቅ አቀባበል ተደረገላቸው።
ብፁዕ አቡነ ናትናኤል በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ኢየሩሳሌም ሲደርሱ ደማቅ አቀባበል ተደረገላቸው።
(#EOTCTV ሐምሌ 26 ቀን 2017 ዓ.ም)
ሪፖርተር ሰላም አምባዬ
++++++++++++++++++++++++++++
በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀጳጳስ ሁነው የተመደቡት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ወደ መንበረ ጵጵስናቸው ሲያቀኑ በብፁዕ አቡነ መልከጼድቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ኃላፊ ሊቀጳጳስ፣ ከጠቅላይ ቤተክህነት የመምርያ ኃላፊዎች ጋር በመሆን ትናንት ቲላቪቮ (ቤን ጎርዮን) ዓለም አቀፍ የአውሮፕላን ማረፍያ ሲደርሱ የገዳሙ መጋቤ የሆኑት መጋቤ አባ ተክለ ሃይማኖት ኃይለ ማርያም እና በርካታ የገዳሙ አበው መነኮሳት በተገኙበት ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል ።
እንዲሁም በደብረ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም ሲደርሱ በከተማው የሚኖሩ ምዕመናን እና መዘምራን ልብሰ ተክህኖ ለብሰው በዝማሬ ከተቀበሏቸው በኋላ ወደ ቤተ መቅደሱ በመግባት እንደ ገዳሙ ሕግና ሥርዓተ ጸሎተ ወንጌል አድርሰዋል ።
በመቀጠልም :- አባ ገብረ ሥላሴ ብፁዕነታቸውን ወደ መንበረ ጵጵስናዎ እንኳን በደህና መጡ ሲሉ ደስታቸውን ገልጸውላቸዋል ።
ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የቀደሙትን አባቶቻችሁን ተመልከቱ በተባለው መሠርት ጥንታውያን አባቶቻችን ዘመን ተሻጋሪ የሆነው ታሪክ አውርሰውናል እኛም የአበው አደራ ጠብቀን ማስጠበቅ ይገባናል ሲሉ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል ።
ብፁዕ አቡነ መልከጼድቅ በበኩላቸው ከቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠንን አደራ ለማስጠበቅ በቅድስትዋ ሀገር ተገኝተናል ሲሉ ደስታቸውን ገልጸዋል ።
ሐምሌ 25 ቀን 2017 ዓ/ም የተከናወነው የአቀባበል መርሐግብር በደብረ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም አብው መነኮሳት ብቻ የተዘጋጀ ሲሆን በቀጣይ ቀናት በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት በጋራ በመሆን የሚያከናውኑት የአቀባበል ሥነ ሥርዓት መርሐግብር እንደሚኖር በዕለቱ ተጠቅሷል ።
ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ቀደም ሲል በሀገረ አሜሪካ የኮሎራዶና አከባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ሆነው ማገልገላቸው ይታወሳል።


