ተማሪዎች በእምነታቸው እንዲጸኑ እና ሕይወታቸው እንዲጠበቅ ቅዱስ ቁርባን መቀበል እንደ ሚገባቸው ተገለጸ፡፡
(MK TV ሚያዚያ 09 2017 ዓ.ም)
በማኅበረ ቅዱሳን አዲስ አበባ ማእከል የሕዝብ ግንኘነትና ትብብር አገልግሎት ዋና ክፍል የዛሬውን የጸሎተ ሐሙስ ቀን ምክንያት በማድረግ ለቅደመ ግቢ ጉባኤ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች የቅዱስ ቁርባን ቅበላ መርሐ ግብር መከናነውን አስታውቋል፡፡
መምህርት ሥራውድንቅ አጥናፍ የመርሐ ግብሩ አስተባባሪ እንደገለጹት የኮተቤ ትምህርት ዩኒቨርሲቲ ሳይንሸርድ ካምፓስ ከአንድ መቶ ሃያ በላይ ለሚሆኑ ከ9 እስከ 12 ክፍል የሚማሩ የቅድመ ግቢ ጉባኤ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ቅዱስ ቁርባንን ተቀብለዋል ብለዋል፡፡
አስተባባሪዋ አክለውም ተማሪዎቹ የክርስቶስን ክቡር ሥጋና ደም በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም እንደተቀበሉ የተናገሩ ሲሆን ይህም መንፈሳዊ መልካም ተግባር በሌሎች የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መስፋፋት እንዳለበት ገልጸዋል፡፡
ቅዱስ ቁርባንን የተቀበሉት ተማሪዎች ተከታታይ የንስሐ ትምህርት የተማሩ እና ከዋናው ማእከል ካሉ 10 እስከ 12 የሚሆኑ የንስሐ አባቶች ተመድቦላቸው ቀኖና የወሰዱ ናቸው ሲሉ አስተባባሪዋ ጠቁመዋል፡፡
መምህርት ሥራውድንቅ በመልእክታቸው ተማሪዎች በእምነታቸው እንዲጸኑ እና ሕይወታቸውን ከሚያበላሹ እንዲሁም ምስቅልቅል ከሚያደርጉ ነገሮች እንዲጠበቁ ቅዱስ ቁርባንን ሥርዓቱን ተከትለው መቀበል እንደሚጠበቅባቸው ተናግረዋል፡፡
በተጨማሪም መምህር ዘላለም ዓለማየሁ ለተማሪዎቹ ጸሎተ ሐሙስን እና ቅዱስ ቁርባንን በተመለከተ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡
